የቀድሞው የ“አል አይን ኒውስ” ጋዜጠኛ፤ በባህር ዳር ከተማ በመከላከያ ሰራዊት አባላት ተይዞ መወሰዱን የዓይን እማኞች ገለጹ

የዜና ትንታኔ

4/14/20232 min read

“አራት ኪሎ ሚዲያ” የተሰኘው የዩቲዩብ መገናኛ ብዙሃን አዘጋጅ የሆነው ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው፤ ዛሬ አመሻሽ ላይ በአማራ ክልል በባህር ዳር ከተማ በመከላከያ ሰራዊት አባላት ተይዞ መወሰዱን የዓይን እማኞች ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናገሩ። የመከላከያ ሰራዊት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ኮሎኔል ጌትነት አዳነ ስለ ጋዜጠኛው መያዝ መረጃ እንደሌላቸው ገልጸዋል። ጋዜጠኛው የስራ አመራር ቦርድ አባል የሆነበት የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች ማህበርም በተመሳሳይ ስለ ዳዊት መያዝ እስካሁን መረጃ እንደሌለው አስታውቋል።

ጋዜጠኛ ዳዊት ዛሬ ረቡዕ ሚያዝያ 4፤ 2015 አመሻሽ ላይ በመከላከያ ሰራዊት አባላት የተያዘው፤ በባህር ዳር ከተማ በሚገኘው ሆምላንድ ሆቴል ከጓደኞቹ ጋር “ሻይ እየጠጣ” ባለበት መሆኑን የዓይን እማኞቹ ገልጸዋል። ጋዜጠኛውን ወዳልታወቀ ቦታ የወሰዱት የመከላከያ ሰራዊት የኮማንዶ አባላት በሁለት “ፓትሮል” ተጭነው የመጡ መሆናቸውን የጠቆሙት የዓይን እማኞቹ፤ ከእነርሱ ውስጥ አንዱ “አንተን እንፈልግሃለን” ብሎ ዳዊትን ይዞት ወደ ተሽከርካሪዎቹ እንደወሰደው አብራርተዋል።

የመከላከያ ሰራዊት አባሉ ዳዊትን ከጓደኞቹ “ነጥሎ” ከወሰደው በኋላ፤ ከሆቴሉ ቅጥር ግቢ ውጭ ከቆሙት ተሽከርካሪዎች ወደ አንደኛው ውስጥ ሲገባ መመልከታቸውንም እማኞቹ አስረድተዋል። ሆኖም በሰዓቱ “ተደናግጠው ስለነበር” በተሽከርካሪዎቹ ውስጥ ያሉት የመከላከያ ሰራዊት አባላት አጠቃላይ ቁጥር ማወቅ አለመቻላቸውንም አክለዋል። ጋዜጠኛው በመከላከያ ሰራዊት ተይዟል መባሉን በተመለከተ ከ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ጥያቄ የቀረበላቸው የመከላከያ ሰራዊት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ኮሎኔል ጌትነት አዳነ፤ ስለጉዳዩ መረጃ እንደሌላቸው ተናግረዋል።

Related Stories